1. ሐዋርያት
ሐዋርያ የሚለው ቃል በግሪክ ቋንቋ «አፖስቶሎስ» የሚል ሲሆን ትርጉሙም «የተላከ» ማለት ነው፡፡ የተላከ ሲባልም ላኪውን በመወከል የላኪውን መልእክት ብቻ በትክክል የሚያስተላልፍ መልእክተኛ ማለት ነው፡፡ ቃሉ በግሪክ ቋንቋ ውስጥ ማንኛውንም ዓይነት መልእክተኛ የሚያመለክት ቢሆንም በዋናነትና በመደበኛነት የሚያገለግለው ግን እግዚአብሔር የላካቸውን ብቻ ነው፡፡
የሃይማኖታችን (የእምነታችን) ሐዋርያ
ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን በተመለከተ «... የሃይማኖታችንን (የእምነታችንን) ሐዋርያና ሊቀካህናት ኢየሱስ ክርስቶስን ተመልከቱ» የሚል ቃል እናነባለን (ዕብ.3፡1)፤ ይህም ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ራሱ በሰውነቱ ሐዋርያ እንደሆነ የሚናገር ቃል ነው፡፡ በእርግጥም እርሱ ስለራሱ ሲናገር «... እኔንም ታውቁኛላችሁ፤ ከወዴትም እንደሆንሁ ታውቃላችሁ፤ እኔም በራሴ አልመጣሁም፤ ነገር ግን እናንተ የማታውቁት የላከኝ እውነተኛ ነው፤ እኔ ግን ከእርሱ ዘንድ ነኝ፤ እርሱ ልኮኛልና አውቀዋለሁ» በማለት እና «እርሱ ላከኝ እንጂ ከራሴ አልመጣሁምና» በማለት ከአብ ዘንድ የተላከ መሆኑን በግልጽ ተናግሯል (ዮሐ.7፡28፤ 8፡42)፡፡ እርሱ በሰውነቱ የሚናገረውም ሆነ የሚያደርገው ሁሉ ከአብ የሰማውንና አብን ደስ የሚያሰኘውን ብቻ ነበር፤ ይህንንም ሲገልጽ «... ዳሩ ግን የላከኝ እውነተኛ ነው፤ እኔም ከእርሱ የሰማሁትን ይህን ለዓለም እናገራለሁ፤ .... አባቴም እንዳስተማረኝ እነዚህን እናገር ዘንድ እንጂ ከራሴ አንዳች እንዳላደርግ በዚያን ጊዜ ታውቃላችሁ፤....» (ዮሐ.8፡26-30) ብሏል፤ እንደዚሁም በሌላ ስፍራ «እኔ ከራሴ አልተናገርሁምና፤ ነገር ግን የላከኝ አብ የምለውን የምናገረውንም ትእዛዝ ሰጠኝ፤ ትእዛዙም የዘላለም ሕይወት እንደሆነች አውቃለሁ፤ ስለዚህ እኔ የምናገረውን አብ እንደነገረኝ እንዲሁ እናገራለሁ» ብሎ የተናገረውን ቃል እናነባለን (ዮሐ.12፡49-50)፡፡ ስለዚህ ከእነዚህ ሁሉ ቅዱሳን ቃላት ጌታ ኢየሱስ በአባቱ የተላከ፣ ከአባቱ የተቀበለውን መልእክት የተናገረ፣ በሰውነቱ ከራሱ ምንም ያላደረገና ያልተናገረ፣ የላኪውን ፈቃድና መልእክት ብቻ ያስተላለፈ የመጀመሪያው ሐዋርያ መሆኑን እንረዳለን፡፡ ይህንንም የሐዋርያነቱን ሥራ የሠራው በምድር ላይ በሥጋ ሲመላለስ ሳለ በነበረው የማስተማር ዘመኑ ነው፤ በገሊላ፣ በሰማርያና በይሁዳ እየተመላለሰ ያስተማረው ትምህርት ሁሉ የሐዋርያነቱ መልእክት ነበር፤ በእርሱ የነቢይነት አገልግሎትንም የምናይ ቢሆንም የሐዋርያነት አገልግሎቱ ከዚያ ይልቅ ጐልቶ ይታይ ነበረ፤ ይህም የሐዋርያነቱ አገልግሎት በሰውነቱ የሚከናወን በመሆኑ በብዙ ምልክቶችና ድንቆች የጸና ነበር፡፡ ጴጥሮስ ለእስራኤል ሰዎች ሲናገር «ራሳችሁ እንደምታውቁ የናዝሬቱ ኢየሱስ እግዚአብሔር በመካከላችሁ በእርሱ በኩል ባደረገው ተአምራትና በድንቆች በምልክቶችም ከእግዚአብሔር ዘንድ ለእናንተ የተገለጠ ሰው ነበረ» ብሎ ስለኢየሱስ መስክሯል (የሐ.ሥ.2፡22)፤ ይህ በእርሱ የተደረገው ምልክት እርሱ ከአብ የተላከ ሐዋርያ መሆኑን አረጋግጦለታል፡፡ የእርሱ የሐዋርያነቱ መልእክቶችና ሥራዎች ሁሉ በ4ቱ ወንጌላት ተመዝግበውልናል፤ በመሆኑም በምድር ላይ ሲመላለስ በፍጹም ሐዋርያነቱ በታማኝነት የአባቱን መልእክት ወደ ሰው ያደረሰውን የእርሱን መልእክት በአግባቡ እንረዳው ዘንድ እንትጋ፡፡
አሥራ ሁለቱ ሐዋርያት
ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ከአብ የተላከ ሐዋርያ ሆኖ የተገለጠ ሰው ነበር፤ ነገር ግን እርሱ የመጀመሪያው ሐዋርያ ብቻ ሳይሆን ሐዋርያትን መምረጥና መላክ የሚቻለው ጌታም ነበር፡፡ የእርሱ የሐዋርያነት አገልግሎቱ የሚያበቃበት ጊዜ እንደሚኖር ስለሚያውቅ ከደቀመዛሙርቱ መካከል አሥራ ሁለት ደቀመዛሙርት መርጦ ሐዋርያት አድርጎ ሲሾማቸውና ሲልካቸው እንመለከታለን፡፡ ይህንንም ያደረገው በእነርሱ ጥያቄ ወይም ፍላጎት መሠረት ሳይሆን ወይም የእነርሱን ማንነት እየተመለከተ የተሻሉትን በመምረጥ ሳይሆን ራሱ የወደዳቸውን ወደ ራሱ ጠርቶ በመለየት ነበር፤ ቊጥራቸውንም 12 ያደረገው በራሱ ውሳኔ ነበር፡፡ ይህንንም ማርቆስ ሲጽፍ «ወደ ተራራም ወጣ፤ ራሱም የወደዳቸውን ወደ እርሱ ጠራ፤ ወደ እርሱም ሄዱ፤ ከእርሱም ጋር እንዲኖሩና ለመስበክ እንዲልካቸው ድውዮችንም ሊፈውሱ አጋንንትንም ሊያወጡ ሥልጣን ይሆንላቸው ዘንድ አሥራ ሁለት አደረገ» በማለት ይገልጻል (ማር3፡13-15)፡፡ ጌታ ኢየሱስ ከደቀመዛሙርቱ መካከል እነዚህን 12ቱን ከለየ በኋላ «ሐዋርያት» ብሎ ሰይሟቸው ነበር፤ ይህንንም ሉቃስ በወንጌሉ ሲጽፍ «በእነዚህም ወራት ይጸልይ ዘንድ ወደ ተራራ ወጣ፤ ሌሊቱንም ሁሉ ወደ እግዚአብሔር ሲጸልይ አደረ፡፡ በነጋም ጊዜ ደቀመዛሙርቱን ጠራ፤ ከእነርሱም አሥራ ሁለት መረጠ፤ ደግሞም ሐዋርያት ብሎ ሰየማቸው፡፡» ብሏል (ሉቃ6፡12-13)፡፡ «ሐዋርያት» ብሎ የሰየመው እነዚህ 12ቱን ብቻ ነው፡፡ ከእነዚህ ከ12ቱ ሌላ ሌሎችን ሰብዓ እንደሾመ ሉቃስ ይነግረናል (ሉቃ10፡1)፤ ሆኖም ሐዋርያት ብሎ አልሰየማቸውም ነበር፡፡ በመሆኑም ጌታ ኢየሱስ ለአሥራ ሁለቱ ሐዋርያት የሰጠው ስፍራ ለየት ያለ ሲሆን የሐዋርያነት ሥራውን እንዲሠሩም ለየት ያለ ሥልጣን እንደሰጣቸው እንረዳለን፡፡
ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ከአብ የተላከ ሐዋርያ ሆኖ የተገለጠ ሰው ነበር፤ ነገር ግን እርሱ የመጀመሪያው ሐዋርያ ብቻ ሳይሆን ሐዋርያትን መምረጥና መላክ የሚቻለው ጌታም ነበር፡፡ የእርሱ የሐዋርያነት አገልግሎቱ የሚያበቃበት ጊዜ እንደሚኖር ስለሚያውቅ ከደቀመዛሙርቱ መካከል አሥራ ሁለት ደቀመዛሙርት መርጦ ሐዋርያት አድርጎ ሲሾማቸውና ሲልካቸው እንመለከታለን፡፡ ይህንንም ያደረገው በእነርሱ ጥያቄ ወይም ፍላጎት መሠረት ሳይሆን ወይም የእነርሱን ማንነት እየተመለከተ የተሻሉትን በመምረጥ ሳይሆን ራሱ የወደዳቸውን ወደ ራሱ ጠርቶ በመለየት ነበር፤ ቊጥራቸውንም 12 ያደረገው በራሱ ውሳኔ ነበር፡፡ ይህንንም ማርቆስ ሲጽፍ «ወደ ተራራም ወጣ፤ ራሱም የወደዳቸውን ወደ እርሱ ጠራ፤ ወደ እርሱም ሄዱ፤ ከእርሱም ጋር እንዲኖሩና ለመስበክ እንዲልካቸው ድውዮችንም ሊፈውሱ አጋንንትንም ሊያወጡ ሥልጣን ይሆንላቸው ዘንድ አሥራ ሁለት አደረገ» በማለት ይገልጻል (ማር3፡13-15)፡፡ ጌታ ኢየሱስ ከደቀመዛሙርቱ መካከል እነዚህን 12ቱን ከለየ በኋላ «ሐዋርያት» ብሎ ሰይሟቸው ነበር፤ ይህንንም ሉቃስ በወንጌሉ ሲጽፍ «በእነዚህም ወራት ይጸልይ ዘንድ ወደ ተራራ ወጣ፤ ሌሊቱንም ሁሉ ወደ እግዚአብሔር ሲጸልይ አደረ፡፡ በነጋም ጊዜ ደቀመዛሙርቱን ጠራ፤ ከእነርሱም አሥራ ሁለት መረጠ፤ ደግሞም ሐዋርያት ብሎ ሰየማቸው፡፡» ብሏል (ሉቃ6፡12-13)፡፡ «ሐዋርያት» ብሎ የሰየመው እነዚህ 12ቱን ብቻ ነው፡፡ ከእነዚህ ከ12ቱ ሌላ ሌሎችን ሰብዓ እንደሾመ ሉቃስ ይነግረናል (ሉቃ10፡1)፤ ሆኖም ሐዋርያት ብሎ አልሰየማቸውም ነበር፡፡ በመሆኑም ጌታ ኢየሱስ ለአሥራ ሁለቱ ሐዋርያት የሰጠው ስፍራ ለየት ያለ ሲሆን የሐዋርያነት ሥራውን እንዲሠሩም ለየት ያለ ሥልጣን እንደሰጣቸው እንረዳለን፡፡
በአራቱ ክፍሎች የተመዘገበው የስም ዝርዝር በቅደም ተከተል አንድ ባይሆንም በዝርዝሩ ውስጥ የተመዘገቡት ሐዋርያት ግን በ4ቱም ክፍሎች ውስጥ እነዚያው ራሳቸው ናቸው፤ «ታዴዎስ የተባለው ልብድዮስ» በሉቃስ ወንጌል «የያዕቆብ ይሁዳ»፣ በሐዋርያት ሥራ ደግሞ «የያዕቆብ ልጅ ይሁዳ» የተባለው ነው፤ አንዳንድ ትርጉሞች ይህን ሐዋርያ በሉቃስ ወንጌልና በሐዋርያት ሥራ ላይ «የያዕቆብ ወንድም ይሁዳ» ይሉታል፡፡ እንዲሁም በማቴዎስና በማርቆስ «ቀነናዊው ስምዖን» የተባለው በሉቃስና በሐዋርያት ሥራ «ቀናተኛ የሚባለው ስምዖን» ብሎ የተገለጠው ነው፡፡
በሐ.ሥራ1፡13 ላይ የተዘረዘሩት ሐዋርያት 11ዱ ብቻ መሆናቸውና 12ኛው የሐዋርያነት ስፍራ ክፍት የነበረው ጌታን አሳልፎ የሰጠው የአስቆሮቱ ይሁዳ ስላልተቆጠረ ነው፡፡ የአስቆሮቱ ይሁዳ ከሐዋርያት ጋር ተቆጥሮ ለዚህ አገልግሎት ታድሎ የነበረ ቢሆንም ጌታን አሳልፎ በመስጠቱ ወደ ገዛ ራሱ ስፍራ ይሄድ ዘንድ የሐዋርያነት ስፍራውን ትቶ ሄደ (የሐ.ሥራ1፡17 እና 25)፤ ሆኖም በምትኩ ማትያስ ከአሥራ አንዱ ሐዋርያት ጋር ተቈጥሮአል (የሐ.ሥራ1፡26)፤ ከዚህ በኋላ በሐዋርያት ሥራ ውስጥም ሆነ ቀጥሎ ባሉት በሌሎች የአዲስ ኪዳን መጻሕፍት ውስጥ አሥራ ሁለቱን ሐዋርያት የሚጠቅስ ንባብ ሲገኝ ማትያስን በመቊጠር እንደሆነ መገንዘብ ይቻላል፡፡
ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ አሥራ ሁለቱን ሐዋርያት ከመጀመሪያው ሲመርጣቸውና ሲሾማቸው ዓላማው ከእርሱ ጋር እንዲኖሩና ለመስበክ እንዲልካቸው ነበር (ማር.3፡14)፡፡ ወደ ዓለም ሁሉ ከመላኩ በፊት እርሱ በምድር እያለ የላካቸው ከእስራኤል ወደ ጠፉት በጎች ብቻ ነበር፤ ይህንንም ሲገልጽ አሥራ ሁለቱን ባሰማራቸው ጊዜ ሲያዝዛቸው «በአሕዛብ መንገድ አትሂዱ፤ ወደ ሳምራውያንም ከተማ አትግቡ፤ ይልቅስ ከእስራኤል ቤት ወደሚሆኑት ወደ ጠፉት በጎች ሂዱ» ብሏቸዋል (ማቴ10፡5-6)፡፡ ሄደው የሚሰብኩትም የእግዚአብሔርን መንግሥት ሲሆን ዋና ይዘቱም «መንግሥተ ሰማያት ቀርባለች» የሚል ነበር (ማቴ.10፡7፤ ሉቃ.9፡2)፡፡ የላካቸውም ሁለት ሁለት አድርጎ ነበር (ማር.6፡7)፤ በርኩሳን መናፍስትና በበሽታ ሁሉ ላይ ሥልጣን ሰጥቷቸውም ነበር፡፡ አገልግሎታቸውን የሚፈጽሙትም እንዴት እንደሆነ መመሪያ ከሰጣቸው በኋላ ላካቸው (ማቴ.10፡5-42)፡፡ ሐዋርያትም በታዘዙት መሠረት አገልግሎታቸውን ፈጽመው ወደ እርሱ ከተመለሱ በኋላ ያደረጉትን ሁሉ ለኢየሱስ ነገሩት (ሉቃ.9፡10)፡፡ ጌታ ኢየሱስም ቢሆን ለእስራኤል የመንግሥትን ወንጌል ይሰብክ ነበር፤ ይሁንና እስራኤላውያን እርሱን በመሢሕነት ካለመቀበላቸውም የተነሣ የሰበከውን የመንግሥት ወንጌል አልተቀበሉም ነበር፤ በዚህም ምክንያት እስራኤል ለጊዜው ወደ ጐን ከተተወች በኋላ የእግዚአብሔር የጸጋ በር ለአሕዛብ ተከፈተ፤ የክርስቶስ ሞት እና ትንሣኤም ለዓለም ሁሉ የመዳን መንገድ ሆነ፡፡ ጌታ ከትንሣኤው በኋላ በአንድ ላይ ለነበሩት 11ዱ ሐዋርያት ሊያርግ ሲል ወደ ዓለም ሁሉ ሄደው እንዲሰብኩ ሲልካቸው እንመለከታለን፤ በማቴ.28፡19 ላይ እንደምናነበው «እንግዲህ ሂዱና አሕዛብን ሁሉ በአብ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ ስም እያጠመቃችኋችው ያዘዝኋችሁንም ሁሉ እንዲጠብቁ እያስተማራችኋቸው ደቀመዛሙርት አድርጓቸው፤ እነሆ እኔ እስከዓለም ፍጻሜ ድረስ ሁል ጊዜ ከእናንተ ጋር ነኝ» ብሏቸዋል፤ እንደዚሁም በማር.16፡15 «ወደ ዓለም ሁሉ ሂዱ ወንጌልንም ለፍጥረት ሁሉ ስበኩ» ብሎ የሰጣቸውን መመሪያ እናነባለን፡፡ ይህም እግዚአብሔር ከአሕዛብ መካከል ለስሙ የሚሆን ወገንን ለመውሰድ የሚያስችለውን መንገድ ይከፍታል፤ ከዚያ በፊት ግን ኢየሱስ ከእነርሱ ሲለይ በምትኩ የሚመጣውን አጽናኝ የሆነውን መንፈስ ቅዱስን መጠበቅ ነበረባቸው፤ ስለሆነም ከመሰማራታቸው በፊት ለሥራቸው ኃይል የሚሆናቸውን መንፈስ ቅዱስን በኢየሩሳለም ሆነው እንዲጠብቁ አዘዛቸው (ሉቃ.2፡49)፡፡ ከዚያ በኋላ ግን ምስክርነታቸው በእስራኤል ብቻ ሳይሆን እስከምድር ዳር ድረስ እንደሚሆን ሲነግራቸው «...ነገር ግን መንፈስ ቅዱስ በእናንተ ላይ በወረደ ጊዜ ኃይልን ትቀበላላችሁ በኢየሩሳሌምም በይሁዳም ሁሉ በሰማርያም እስከምድር ዳርም ድረስ ምስክሮቼ ትሆናላችሁ» ብሏቸዋል (የሐ.ሥራ1፡8)፡፡ በዚህም መሠረት ሐዋርያት በመንፈስ ቅዱስ መውረድ ኃይልን ተቀብለው ለእስራኤልና ለአሕዛብ በሰበኩት ወንጌል ከሁለቱ አንድ አዲስ ሰው (አካል) ተፈጠረ ወይም ተመሠረተ (ኤፌ.2፡15)፡፡ ያም አንድ አካል ሌላ ምንም ሳይሆን ቤተክርስቲያን ናት (ኤፌ.1፡23፤ ቈላ.1፡18)፡፡
በሐዋርያት ሥራ መጽሐፍ ውስጥ 12ቱ ሐዋርያት በመጀመሪያ በእስራኤል ምድር በኢየሩሳሌምና በዙሪያዋ ሲያገለግሉ እናገኛቸዋለን፤ በበዓለ ሃምሳ ዕለት ጴጥሮስ ከአሥራ አንዱ ጋር ቆሞ ስለክርስቶስ ሲመሰክር እንደነበር እናያለን (2፡14)፤ ቤተክርስቲያን ከተመሠረተችበት ከዚህ ዕለት ጀምሮ የመጀመሪያዎቹ አማኞች ከሚተጉባቸው ነገሮች ዋናው «የሐዋርያት ትምህርት» ነበር (2፡42)፤ ሐዋርያት በኢየሩሳሌም ሳሉ «የጌታን የኢየሱስ ክርስቶስን ትንሣኤ በታላቅ ኃይል ይመሰክሩ ነበር፤ በሁሉም ላይ ታላቅ ጸጋ ነበረባቸው» (4፡33)፤ አማኞች ከመሬትና ከቤት ሽያጭ የሚያገኙትን ገንዘብ በሐዋርያት እግር አጠገብ ያስቀምጡ ነበር (4፡34፣37፤ 5፡2)፤ በሐዋርያትም እጅ ብዙ ምልክትና ድንቅ በሕዝብ መካከል ይደረግ ነበር (5፡12)፤ ይህም የጌታ ሐዋርያት እንደሆኑ ለሕዝቡ የሚመሰክር ነበር፡፡ በአንድ ላይም ከሚሰጡት የወንጌል ምስክርነት የተነሣ በአንድ ላይ ወደ ወኅኒ ይጣሉ ነበር (5፡18)፤ በኢየሱስ ስም እንዳያስተምሩ ሲታዘዙ ጴጥሮስና ሐዋርያት «ከሰው ሁሉ ይልቅ ለእግዚአብሔር ልንታዘዝ ይገባናል» ይሉ ነበር (4፡19፤ 5፡29)፡፡ ዕለት ዕለትም በመቅደስና በቤታቸው ስለ ኢየሱስ እርሱ ክርስቶስ እንደሆነ ማስተማርንና መስበክን አይተውም ነበር (5፡42)፡፡ በኢየሩሳሌም ባለች ቤተክርስቲያን ለነበረው የማዕድ አገልግሎት ሰባት ሰዎችን አስመርጠው እንደሾሙም እናነባለን፤ ስለራሳቸውም «እኛ ግን ለጸሎትና ቃሉን ለማገልገል እንተጋለን» ብለዋል (የሐ.ሥራ6፡1-6)፡፡ ይህም ሐዋርያት በመጀመሪያ አካባቢ ቤተክርስቲያንን የማስተዳደሩም ሆነ የጸሎትና የቃሉ አገልግሎት በእነርሱ ላይ እንደ ነበረና በኋላ ግን በጸሎትና በቃሉ አገልግሎት ብቻ ሊተጉ ባሉ ጊዜ ሌላውን አገልግሎት ወደ ሌሎች ወንድሞች እንዳስተላለፉ እናያለን፡፡
ሐዋርያት በኢየሩሳሌም እያሉ ከእነርሱ ቀጥሎ ጌታ በሐዋርያነት የሾመውን በኋላ ጳውሎስ የተባለው ሳውልን በበርናባስ አማካኝነት እንደተዋወቁና እንደተቀበሉት እናነባለን (የሐ.ሥራ9፡27)፡፡ ከዚያም በዚያው በእስራኤል አገር ማለትም በይሁዳ ሁሉና በገሊላ በሰማርያም ስለነበሩ አብያተክርስቲያናት መታነጽና መብዛት ስለምናነብ (9፡31) ሐዋርያት በዚያው በምድረ እስራኤል የሠሩት የሐዋርያነት ሥራ ምን ያህል ሰፊ እንደነበር እንገነዛባለን፡፡ ከሐዋርያት መካከል ጴጥሮስ በየስፍራው ሲዞር በልዳና በሰሮና በኢዮጴም ወንጌልን እየሰበከ ሳለ እግዚአብሔር ለአሕዛብ የመዳን ወንጌል የሚደርስበትን መንገድ አዘጋጀ፤ በቂሣርያ የነበረ ቆርኔሌዎስ የሚሉት አንድ መቶ አለቃ ከዘመዶቹና ከቅርብ ወዳጆቹ ጋር ሆኖ ጴጥሮስ ስለክርስቶስ የመሰከረላቸውን ቃል ሲሰሙ በሁሉም ላይ መንፈስ ቅዱስ ወረደ፤ ይህም ልክ በመጀመሪያ የበዓለ ሃምሳ ዕለት እንደወረደው ያለ ሲሆን አሕዛብ ወደ ክርስቶስ አካል በመንፈስ ቅዱስ የተጠመቁበት ጊዜ ነበር (10፡40-48፤ 11፡15-18፤ 15፡7፤ 1ቆሮ12፡13)፡፡ ሐዋርያትና በይሁዳ የነበሩት ወንድሞች አሕዛብ የእግዚአብሔርን ቃል እንደተቀበሉ በሰሙ ጊዜ ጴጥሮስ ወደ አሕዛብ ቃሉ ይደርስ ዘንድ እግዚአብሔር እርሱን የመራው እንዴት እንደነበርና መንፈስ ቅዱስም እንዴት እንደወረደላቸው ሲተርክላቸው እግዚአብሔርን አከበሩ (11፡1-18)፤ ከዚህም በተጨማሪ ሐዋርያት በጳውሎስና በበርናባስ ወንጌል ለአሕዛብ እንዴት እንደደረሰ ከራሳቸው ከጳውሎስና ከበርናባስ ሰምተዋል፤ እንዲያው አሕዛብን «እንደ ሙሴ ሥርዓት ካልተገረዛችሁ ትድኑ ዘንድ አትችሉም» በሚለው የስህተት ትምህርት ምክንያት ሐዋርያት ከሽማግሌዎች ጋር በመሰብሰብ እንደ እግዚአብሔር ቃል ተመካክረው የአሕዛብን ወደ ቤተክርስቲያን መግባት በይፋ የሚያረጋግጥ ውሳኔ ላይ ደርሰዋል፡፡ «እኛና መንፈስ ቅዱስ ፈቅደናል» በሚለው የውሳኔያቸው ቃል የምንረዳው እነርሱ የሚሠሩትም ሆነ የሚወስኑት ሙሉ በሙሉ በመንፈስ ቅዱስ ምሪትና ኃይል እንደሆነ ነው (የሐ.ሥራ15፡1-29)፡፡ ከዚህ በኋላ ውሳኔውን ይዘው ወደ አንጾኪያ የሄዱት ወንድሞች አያሌ ቀን ተቀምጠው እስኪመለሱ ድረስ ሐዋርያት በኢየሩሳሌም እንደነበሩ ለማወቅ እችላለን (15፡33)፡፡ ከዚህ አስቀድሞ ግን ከሐዋርያት መካከል የዮሐንስ ወንድም ያዕቆብ በሄሮድስ ሰይፍ ተገድሏል (12፡2)፤ ጴጥሮስም በወኅኒ ታስሮ የነበረ ቢሆንም ጌታ ከእስር ቤት አወጣው፤ ከዚያም በቤተክርስቲያን ስለ እርሱ ይጸልዩ ለነበሩት ጌታ ከወኅኒ እንዴት እንዳወጣው ከተረከላቸው በኋላ ወጥቶ ወደ ሌላ ስፍራ ሄዶ ነበር (12፡3-17)፤ ይሁንና በሐ.ሥራ15 ላይ በምናነበው አሕዛብን በተመለከተ በነበረው የሐዋርያት ስብሰባ ላይ ተገኝቶ ነበር፡፡ ከዚህ በኋላ ሐዋርያት በአንድ ላይ ሆነው ሥራ ሲሠሩ የሚገልጽ ንባብ አናገኝም፡፡
ከዚህ በኋላ እያንዳንዳቸው የተሰማሩባቸውን ስፍራዎችና የሠሩአቸውን ሥራዎች እንዲሁም የእያንዳንዳቸው ፍጻሜ ምን እንደሆነ ከመጽሐፍ ቅዱስ የምናውቀው ነገር የለም፤ ሆኖም የወደፊት ክብራቸውን በሚገባ እናውቃለን፤ ጴጥሮስ ጌታ ኢየሱስን «እነሆ እኛ ሁሉን ትተን ተከተልንህ፤ እንኪያስ ምን እናገኝ ይሆን?» ብሎ በጠየቀው ጊዜ «እውነት እውነት እላችኋለሁ፤ እናንተስ የተከተላችሁኝ በዳግመኛ ልደት የሰው ልጅ በክብሩ ዙፋን በሚቀመጥበት ጊዜ እናንተ ደግሞ በአሥራ ሁለቱ የእስራኤል ነገድ ስትፈርዱ በአሥራ ሁለት ዙፋን ትቀመጣላችሁ» የሚል የከበረ ተስፋን ተቀብሏል (ማቴ19፡27-28)፤ ይህም ጌታ በሺው ዓመት የክብር መንግሥት ጊዜ ለሐዋርያት የሚሰጠውን የተለየ ዙፋንና ክብር ያመለክታል፡፡ በራእ.21፡14 ላይ የእግዚአብሔር ክብር ላለባት ለቅድስቲቱ ከተማ ለአዲሲቱ ኢየሩሳሌም ባሏት አሥራ ሁለት መሠረቶች ላይ አሥራ ሁለቱ የበጉ ሐዋርያት ስሞች ተጽፈው እንደ ነበር ይናገራል፤ 12ኛው ስምም በይሁዳ ፈንታ የተተካው የማትያስ ስም እንደሆነ ጥርጥር የለውም፡፡ ይህም በሺው ዓመት መንግሥት ከክርስቶስ ጋር አብራ በምትነግሠውና በምትገዛው ቤተክርስቲያን ውስጥ ያላቸውን የመሠረት (ዋነኛ የሆነ) ስፍራ ያመለክታል፡፡
የጳውሎስ ሐዋርያነት
ጌታ ኢየሱስ ካረገና በክብር በአብ ቀኝ ከተቀመጠ በኋላ ሐዋርያ አድርጎ የሾመው ጳውሎስን ብቻ ነው፡፡ ጳውሎስ የቀድሞ ስሙ ሳውል ይባል የነበረ ሲሆን ክርስቶስን ከማመኑ በፊት ቤተክርስቲያንን ያለልክ የሚያሳድድ ከብንያም ነገድ የሆነ አይሁዳዊ ሕግንም ከሁሉ አስበልጦ የሚያጠብቅ ፈሪሳዊ ነበር (የሐ.ሥራ8፡3፤ 26፡9-11፤ ገላ.1፡13-14፤ ፊልጵ.3፡5-6)፤ ነገር ግን ይህን ያደርግ የነበረው ባለማወቅ ነበር (1ጢሞ.1፡13)፤ እንዲያውም የናዝሬቱን ኢየሱስን ስም የሚቃወም እጅግ ነገር ያደርግ ዘንድ የሚገባው ይመስለው ነበር (የሐ.ሥራ26፡9)፤ በዚያን ጊዜ እርሱ ለእግዚአብሔር ቀናተኛ የነበረ አይሁዳዊ ሰው ነበር (የሐ.ሥራ22፡3)፤ ቤተክርስቲያንን ማሳደዱም ለእግዚአብሔር ካለው ቅንዓት የተነሣ ነበር (ፊልጵ.3፡6፤ የሐ.ሥራ22፡3)፡፡ በዚህ ዓይነት የጌታን ደቀመዛሙርት ለማሳደድ ወደ ደማስቆ በመሄድ ላይ ሳለ በሰማይ የከበረው የናዝሬቱ ኢየሱስ በመንገድ ላይ በክበር ታየው (የሐ.ሥራ9፡1-9)፤ ጌታ ለሳውል በክብር የታየበት ምክንያት ሳውል በእርሱ እንዲያምን ለመጥራት ብቻ ሳይሆን ለአገልግሎት ሊሾመውም ነበር፡፡ ይህንንም ራሱ ሲነግረው «ስለዚህ እኔን ባየህበት ነገር ለአንተም በምታይበት ነገር አገልጋይና ምስክር ትሆን ዘንድ ልሾምህ ታይቼልሃለሁና» ብሎታል (የሐ.ሥራ26፡16)፡፡ ስለሆነም ጳውሎስ ለአገልግሎት የተሾመው በቀጥታ በራሱ በጌታ በኢየሱስ ነው፡፡ በዚህ ነገር ጳውሎስ ጌታን ሲያመሰግን «ለአገልግሎቱ ሾሞኝ ታማኝ አድርጎ ስለቈጠረኝ ኃይል የሰጠኝን ክርስቶስ ኢየሱስን ጌታችንን አመሰግናለሁ» ብሏል (1ጢሞ.1፡12)፡፡ አገልግሎቱም የሐዋርያነት አገልግሎት ነው፤ ጳውሎስ ጌታ በደማስቆ በታየው ዕለት የተጠራው አማኝ እንዲሆን ብቻ ሳይሆን ሐዋርያ እንዲሆንም ነው፤ እርሱ በሮሜ1፡1 ላይ ስለራሱ ሲጽፍ «ሐዋርያ ሊሆን የተጠራ...» ብሏል፡፡ ስለዚህ ጥሪው ለማመን ብቻ ሳይሆን ለሐዋርያነትም ነበር፡፡ ጌታ ለየት ባለ ሰማያዊ ክብሩ ሊታየው ያስፈለገውም ለሐዋርያነት አገልግሎት ሊሾመው ስለወደደ ነው እንጂ ለማመን ብቻ ቢሆን ኖሮ እንደማንኛውም ሰው ሊያምን የሚችልበት ሌላ ብዙ መንገድ ነበር፡፡ ጌታም የሾመው በዋናነት የአሕዛብ ሐዋርያ አድርጎ ነበር፡፡ ይህንንም ራሱ ሲገልጥ «ለተገረዙት ሐዋርያ እንዲሆን ለጴጥሮስ የሠራለት ለእኔ ደግሞ ለአሕዛብ ሐዋርያ እንድሆን ሠርቷልና» ብሏል (ገላ.2፡8)፤ በሮሜ11፡14 ላይም «እኔ የአሕዛብ ሐዋርያ እንደመሆኔ መጠን...» እያለ ሲጽፍ እናገኛለን፡፡ በክርስቶስ አካል ውስጥ አሕዛብ የመግባታቸው ምስጢርም የተገለጠው ለዚሁ የአሕዛብ ሐዋርያ ለሆነው ለጳውሎስ ነው (ኤፌ.3፡1-9)፡፡ ከመጀመሪያም ቢሆን ጌታ ሲልከው «ሂድ እኔ ወደ አሕዛብ ከዚህ ወደ ሩቅ እልክሃለሁና» ብሎት ነበር (የሐ.ሥራ22፡21)፡፡
ጳውሎስ ለጌታ «የተመረጠ ዕቃ» ነው፡፡ ይህንንም ጌታ ለሐናንያ ሲነግረው «ይህ በአሕዛብም በነገሥታትም በእስራኤልም ልጆች ፊት ስሜን ይሸከም ዘንድ ለእኔ የተመረጠ ዕቃ ነው» ብሏል (የሐ.ሥራ9፡15)፡፡ ስለሆነም ጳውሎስ ለጌታ ልዩ ሐዋርያ ነው ማለት ይቻላል፤ በእርግጥም ጌታ በጳውሎስ በኩል ብቻ የገለጣቸው እስከዚያን ጊዜ ድረስ ተሰውረው የነበሩ ምስጢራት አሉ፤ አሕዛብ በቤተክርስቲያን አብረው የክርስቶስ አካል የመሆናቸው እውነት (ኤፌ.3፡1-12)፣ ጌታ የእርሱ የሆኑትን ሊወስድ ሲመጣ በሕይወት ያሉት አማኞች እርሱን ወደ መምሰል በቅጽበተ-ዓይን እንደሚለወጡ (1ቆሮ15፡52)፣ አሁን በእስራኤል ድንዛዜ የሆነው የአሕዛብ ሙላት እስኪገባ ድረስ እንደሆነና ወደፊት ግን እስራኤል ሁሉ እንደሚድን (ሮሜ11፡25-26) የሚናገሩ ምስጢራት ሁሉ የተገለጡት በጳውሎስ በኩል ነው፡፡ ስለሆነም ጳውሎስ ይህን ሁሉ ምስጢር ለሰዎች ይናገር ዘንድ በእግዚአብሔር ፈቃድ ሐዋርያ የሆነ ሰው ነው፤ እነዚህንም ምስጢራት በጻፋቸው መልእክታት የገለጣቸው በመሆኑ ሁሉንም ልናውቃቸው ችለናል፡፡
ከ12ቱ ሐዋርያት እና ከጳውሎስ ሌላስ?
ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ አካሉ ለምትሆን ለቤተክርስቲያን ራስ ተደርጎ የተሰጠው ወደ ላይ ካረገና በአባቱ ቀኝ ከተቀመጠ በኋላ ነው፤ ጳውሎስ በኤፌሶን መልእክቱ ይህን ሲገልጥ «ክርስቶስን ከሙታን ሲያስነሣው ከአለቅነትና ከሥልጣንም ከኃይልም ከጌትነትም ሁሉ በላይና በዚህ ዓለም ብቻ ሳይሆን ነገር ግን ሊመጣ ባለው ዓለም ደግሞ ከሚጠራው ስም ሁሉ በላይ በሰማያዊ ስፍራ በቀኙ ሲያስቀምጠው በክርስቶስ ባደረገው ሥራ የብርታቱ ጉልበት ይታያል» ካለ በኋላ «ሁሉን ከእግሩ በታች አስገዛለት ከሁሉ በላይ ራስ እንዲሆን ለቤተክርስቲያን ሰጠው» ይላል (ኤፌ.1፡21-22)፡፡ ከዚያም ከትንሣኤ በኋላ ባለው በከበረው ሰውነቱ በአባቱ ቀኝ ተቀምጦ ካለበት ለሰዎች ስጦታን እንደሰጠና አንዳንዶችን ሐዋርያት፣ ሌሎችን ነቢያት፣ ሌሎችን ወንጌል ሰባኪዎች፣ ሌሎችን እረኞችና አስተማሪዎች እንዲሆኑ እንደሰጠ ተመልክተናል (ኤፌ.4፡7-11)፡፡ በ1ቆሮ.11፡27-28 ላይም «እናንተ የክርስቶስ አካል ናችሁ፤ እያንዳንዶችሁም ብልቶች ናችሁ» ካለ በኋላ «እግዚአብሔርም በቤተክርስቲያን አንዳንዶቹን አስቀድሞ ሐዋርያትን፣ ሁለተኛም ነቢያትን፣ ሦስተኛም አስተማሪዎችን ... አድርጎአል» ይላል፡፡ ጌታ ለቤተክርስቲያን የሰጣቸውን አገልጋዮች በተመለከተ በሚናገሩት በእነዚህ ክፍሎች «ሐዋርያት» በቅድሚያ ተጠቅሰው እናገኛለን፡፡ ቤተክርስቲያን ከመመሥረቷ በፊት 12ቱ ሐዋርያት የተመረጡና የተሾሙ ቢሆንም ለቤተክርስቲያን ሊሰጡ የሚችሉት ግን እርሷ ከተመሠረተች በኋላ ነው፤ ቤተክርስቲያን የተመሠረተችው ደግሞ ከጌታ ዕርገት በኋላ በበዓለ ሃምሳ ዕለት ነው፡፡ ስለሆነም 12ቱ ሐዋርያትንም ቢሆን ወደ ላይ የወጣውና የቤተክርስቲያን ራስ የሆነው ክርስቶስ ለቤተክርስቲያን ሰጠ ሊባል ይችላል፡፡ እርሱ በምድር እያለ ሐዋርያነታቸው በእስራኤል ዘንድ የተወሰነ እንደነበርና ወደ አሕዛብ ሁሉ እንዲሄዱ ያዘዛቸው ሊያርግ ሲል እንደነበር ቀደም ሲል አይተናል፤ ስለሆነም እነርሱም ቢሆኑ ለቤተክርሰቲያን የተሰጡት ከጌታ ዕርገት በኋላ ነው፤ እዚህ ላይ አሥራ ሁለተኛው ሐዋርያ ማትያስ መሆኑን ማስተዋል ይገባል፡፡ ማትያስ ቀደም ሲል በነበረውና ይሁዳ በተወው የሐዋርያት ስፍራ ገብቶ ከ11ዱ ሐዋርያት ጋር የተቆጠረው ቤተክርስቲያን ከተመሠረተችበት ከበዓለ ሃምሳ በፊት በመሆኑ ለቤተክርስቲናያን የተሰጠው ጌታ በምድር እያለ ከሾማቸው ከ11ዱ ሐዋርያት ጋር 12ኛ ሆኖ እንደሆነ ግልጽ ነው፡፡ ጳውሎስን በተመለከተ ግን የተሾመውም ሆነ ለቤተክርስቲያን ሐዋርያ ሆኖ የተሰጠው ቤተክርስቲያን ከተመሠረተችና ብዙ ካሳደዳት በኋላ መሆኑ የታወቀ ነው፡፡ ስለሆነም በ1ቆሮ.11፡28 እና በኤፌ.4፡11 ላይ የተጠቀሱት ሐዋርያት እነዚሁ 12ቱ ሐዋርያትና ጳውሎስ ናቸው፡፡ እዚህ ላይ መታወቅ ያለበት ነገር በእነዚህ ጥቅሶች ላይ የተጠቀሱት ስጦታዎች ሁሉ በየአጥቢያ ቤተክርስቲያኑ ብቻ ተወሰነው እንዲያገለግሉ ለየአጥቢያ ቤተክርስቲያናቱ የተሰጡ ሳይሆኑ በአጠቃላይ ለመላዋ ቤተክርስቲያን የተሰጡ መሆናቸው ነው፡፡ በዚህም መሠረት ሐዋርያትን ለቤተክርስቲያን ሰጠ ሲባል የክርስቶስ አካል ለሆነችው ለመላዋ ቤተክርስቲያን ሰጠ ማለት ነው እንጂ በዚያን ጊዜም ቢሆን በየአጥቢያ ቤተክርስተያናቱ ሐዋርያት ተሰጥተው ነበር ማለት አይደለም፤ እንደዚሁም ጌታ ተመልሶ እስኪመጣ ድረስ በየስፍራው በሚመሠረቱ አጥቢያ ቤተክርስቲያናት ሐዋርያት ይነሣሉ ማለት አይደለም፤ የመጀመሪያዎቹ ሐዋርያት ሐዋርያነታቸው ለመላው አንዲት የክርስቶስ አካል በመሆኑ ዛሬም ቢሆን የእኛም ሐዋርያት ናቸው፤ እነርሱ በአካል ባይኖሩም ትምህርታቸው የእግዚአብሔር እስትንፋስ በሆነው በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ስለተካተተ ዛሬም እኛ የሐዋርያነታቸው አገልግሎት ተጠቃሚ ነን፡፡
እነዚህ ሐዋርያት ለቤተክርስቲያን ሐዋርያት ሆነው እንዲሰጡ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስን በዓይን ሊያዩት እና የትንሣኤው የዓይን ምስክር ሊሆኑ ግድ ነበር፤ ይህም ብቻ ሳይሆን ጌታን ካዩትና የትንሣኤው የዓይን ምስክር ከሆኑትም መካከል ሐዋርያ የሚሆኑት ጌታ ሐዋርያ አድርጎ የሾማቸው ብቻ ናቸው፡፡ ይህም ማትያስ እና ጳውሎስ ሐዋርያ ተደርገው ከተመረጡበትና ከተሾሙበት ታሪክ በግልጽ የምንረዳው እውነት ነው፡፡
- 1ኛ) ማትያስ፡- ይሁዳ ትቷት ለሄደው የሐዋርያነት ስፍራ ማትያስ እና ዮሴፍ የተባለው ደቀመዘሙር የተመረጡት ጌታ እስካረገበት ቀን ድረስ ከጌታና ከሐዋርያት ጋር አብረው የነበሩ ስለሆነ ነው፤ ይህንን ጴጥሮስ ሲናገር «ስለዚህ ከዮሐንስ ጥምቀት ጀምሮ ከእኛ ዘንድ እስካረገበት ቀን ድረስ ጌታ ኢየሱስ በእኛ መካከል በገባበትና በወጣበት ዘመን ሁሉ ከእኛ ጋር አብረው ከነበሩት ሰዎች ከእነዚህ አንዱ ከእኛ ጋር የትንሣኤው ምስክር ሊሆን ይገባል» ብሎአል (የሐ.ሥራ1፡22)፡፡ እነዚህ ሰዎች ከመጥምቁ ዮሐንስ ጀምሮ አብረው ስለነበሩ ጌታን ከሞቱ አስቀድሞ በማስተማር ዘመኑ ሁሉ በማየታቸው ላደረገውና ላስተማረው ምስክር መሆን ይችላሉ፤ እንዲሁም ጌታ እስካረገበት ቀን ድረስ አብረው የነበሩ ስለሆኑ የክርስቶስ የትንሣኤው ምስክር መሆን ይችላሉ፤ ይህ የመጀመሪያውና የሐዋርያነቱን ስፍራ ለመያዝ መሟላት የነበረበት ነገር ነው፡፡ ሆኖም የነበረው የሐዋርያነት ስፍራ ይሁዳ ትቶት የሄደው አንድ ስፍራ ብቻ ነበር፤ ለዚያም ስፍራ ከሁለቱ ሰዎች አንዱን መርጦ መሾም የሚችለው ጌታ ብቻ ነው፤ በመሆኑም እነ ጴጥሮስ ሲጸልዩ «የሁሉን ልብ የምታውቅ አንተ ጌታ ሆይ ይሁዳ ወደ ገዛ ራሱ ስፍራ ይሄድ ዘንድ በተዋት በዚህች አገልግሎትና ሐዋርያነት ስፍራን እንዲቀበል የመረጥኸውን ከእነዚህ ከሁለቱ አንዱን ሹመው» ለማለት ችለዋል፡፡ የተጣጣሉትም ዕጣ ለማትያስ በመውደቁ ጌታ የሾመው ማትያስን መሆኑ ስለተረጋገጠ እርሱ ከአሥራ አንዱ ሐዋርያት ጋር ተቈጠረ (የሐ.ሥራ1፡25-26)፡፡ ዮሴፍ ግን ጌታ ኢየሱስ በምድር ሳለ በገባበትና በወጣበት ዘመን ሁሉ ከሐዋርያት ጋር አብሮ የነበረና የትንሣኤውም የዓይን ምስክር ቢሆንም ሐዋርያ ሳይሆን ቀርቷል፡፡ ይህም በጌታ ሐዋርያ ተደርጎ ባለመሾሙ ነበር፡፡ ስለሆነም ሐዋርያ ለመሆን ጌታን ከማየትና የትንሣኤው የዓይን ምስክር ከመሆን በተጨማሪ በራሱ በጌታ መሾም የግድ ነው፡፡
- 2ኛ) ጳውሎስ፡- ይህ ሐዋርያ በተጠራ ጊዜ በደማስቆ መንገድ ላይ ጌታን አይቶታል፤ በአብ ቀኝ በክብር የተቀመጠው ጌታ ኢየሱስ ለእርሱ ከታየበት ምክንያትም ዋናው እርሱን ሐዋርያ አድርጎ ሊሾመው ነው፤ ይህንንም ጌታ «እኔን ባየህበት ነገር ለአንተም በምታይበት ነገር አገልጋይና ምስክር ትሆን ዘንድ ልሾምህ ታይቼልሃለሁ» ብሎ እንደነገረው ተመልክተናል (የሐ.ሥራ26፡16)፡፡ በኋላም ጳውሎስ በአገልግሎት ዘመኑ የእርሱን ሐዋርያነት ያልተቀበሉ ሰዎች ለሚናገሩበት ተቃውሞ በሰጠው መልስ ላይ ጌታን ማየቱን የሐዋርያነቱ ማስረጃ አድርጎ ሲያቀርብ እንመለከታለን፤ ይህንንም በ1ቆሮ9፡1 ላይ «እኔ ነጻ አይደለሁምን? ሐዋርያስ አይደለሁምን? ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን አላየሁትምን?» በማለት ይገልጸዋል፡፡ ለገላትያ ሰዎች በጻፈው መልእክት ውስጥም «በኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታንም ባነሣው በእግዚአብሔር አብ ሐዋርያ የሆነ እንጂ ከሰዎች ወይም በሰው ያልሆነ ጳውሎስ» ብሎ ራሱን ይገልጣል (1፡1)፡፡ የሚሰብከውንም ወንጌል የተቀበለው በቀጥታ ከጌታ እንደሆነ ሲያስረዳ «ወንድሞች ሆይ በእኔ የተሰበከ ወንጌል እንደሰው እንዳይደለ አስታውቃችኋለሁ፤ አየሱስ ክርስቶስ ገልጦልኛል እንጂ እኔ ከሰው አልተቀበልኩትም አልተማርሁትምም» ብሏል (ገላ.1፡11-12)፡፡ ጳውሎስ በቀጥታ ጌታን ያየና በጌታ የተሾመ የሚሰብከውንም በቀጥታ ከጌታ የተቀበለ ከመሆኑም በላይ የትንሣኤው ምስክር መሆንም ችሏል፤ ምክንያቱም እርሱ ጌታን ያየው ከትንሣኤ በኋላ ባለው ማንነቱ ስለሆነ ነው፤ ክርስቶስ ከተነሣ በኋላ ለተለያዩ ሰዎች ለሐዋርያትም ከታየ በኋላ በመጨረሻ ለእርሱ መታየቱን በመግለጽ ይህን ከሐዋርያነቱ ጋር ሲያያይዘው «ከዚያ በኋላ እንደ ጭንጋፍ ለምሆን ለእኔ ደግሞ ታየኝ፡፡ እኔ ከሐዋርያት ሁሉ የማንስ ነኝና የእግዚአብሔርን ቤተክርስቲያን ስላሳደድሁ ሐዋርያ ተብዬ ልጠራ የማይገባኝ ነገር ግን በእግዚአብሔር ጸጋ የሆንኩ እኔ ነኝ» በማለት ጽፏል (1ቆሮ.15፡7-9)፡፡
>በመሆኑም በመጽሐፍ ቅዱስ ሐዋርያት ተብለው የተጠሩትና ጌታም ሐዋርያት አድርጎ የሾማቸው እነዚሁ ከላይ የተጠቀሱት 12ቱ ሐዋርያትና ጳውሎስ ብቻ ናቸው፡፡
ሌሎች ሐዋርያት እንዳሉ የሚናገሩ ጥቅሶች የሉምን?
በመቀጠል ደግሞ ሌሎች ሐዋርያት እንዳሉ የሚናገረውን የሰው ትምህርት ተቀባይነት ያለው ለማድረግ ሲባል አንዳንዶች የሚጠቅሷቸውን ጥቅሶችን በማንሳት ቃሉ የሚናገረውን እውነት ማጥናቱ አግባብነት ስላለው በመቀጠል እንመለከታቸዋለን፡፡
- ሀ. የሐ.ሥራ14፡4፣14
በዚህ ንባብ ውስጥ እንደምንመለከተው ጳውሎስና በርናባስ አንድ ላይ ከመሥራታቸው የተነሳ በአንድ ላይ ሐዋርያት ተብለው ተጠርተዋል፡፡ በርናባስ በትውልዱ የቆጵሮስ ሰው ቢሆንም በወገኑ ሌዋዊ የሆነ አይሁዳዊ ነበር፤ በኢየሩሳሌም ከነበሩ የመጀመሪያዎቹ አማኞች አንዱ ሲሆን የቀድሞ ስሙ ዮሴፍ ይባል ነበር፡፡ በርናባስ ተብሎ የተሰየመው በሐዋርያት ነው፡፡ የነበረውንም እርሻ ሸጦ ገንዘብን አምጥቶ በሐዋርያት እግር አጠገብ ያኖረ ሰው ነበር (የሐ.ሥ4፡36-37)፡፡ ስለ በርናባስ የምናነበው የመጀመሪያ ነገር ይህን ብቻ ነው፡፡ ይህም በርናባስ ለወንጌል ሥራ የተለየ ሰው እንደ ነበር ያመለክተናል፤ በመሆኑም በአንጾኪያ ቊጥራቸው እጅግ የሚሆን ሰዎች አምነው ወደ ጌታ ዘወር እንዳሉ ወሬው በኢየሩሳሌም ቤተክርስቲያን እንደተሰማ በርናባስ ለአገልግሎት ወደ አንጾኪያ እንደተላከ እናነባለን፤ እርሱም ሳውልን (ጳውሎስን) ተሰዶ ከሄደበት ከጠርሴስ አምጥቶ ለአንድ ዓመት ያህል አብረው ሕዝብን አስተምረዋል (የሐ.ሥራ11-20-26)፡፡ ቀደም ሲል ሳውልን ጌታ ከታየውና ከጠራው በኋላ ወደ ሐዋርያት ያገባውና ያስተዋወቀው ይኸው በርናባስ ነበር (የሐ.ሥ9፡27)፡፡ በርናባስና ሳውል በአንጾኪያ ወንጌልን ማስተማር ከጀመሩ በኋላ ደግሞ አብረው ሲያገለግሉ እናያለን፡፡ በቀላውዴዎስ ቄሣር ዘመን በዓለም ላይ በነበረው ታላቅ ረሃብ ጊዜ የአንጾኪያ አማኞች በይሁዳ ለሚኖሩት ወንድሞች እርዳታን የላኩት በበርናባስና በሳውል (ጳውሎስ) እጅ ነበር (የሐ.ሥራ11፡27-30)፡፡ ይህን አገልግሎታቸውን ፈጽመው ማርቆስን ይዘው ከኢየሩሳሌም ወደ አንጾኪያ ከተመለሱ በኋላ በዚያ ከነበሩ ነቢያትና መምህራን ጋር ጌታን እያመለኩ ሲጦሙ መንፈስ ቅዱስ «በርናባስና ሳውልን ለጠራኋቸው ሥራ ለዩልኝ» አለ (የሐ.ሥራ11፡25-13፡3)፤ ከዚህ በኋላ ጳውሎስ በቆጵሮስና በታናሽ እስያ ያደረገውን የመጀመሪያ የወንጌል ጉዞ የተጓዘውና ሐዋርያዊ ሥራውን የሠራው ከበርናባስ ጋር ነበር፡፡ የሐዋርያት ሥራ መጽሐፍ በዚህ ጉዞ ውስጥ በኢቆንዮን ስለጌታ እጅግ ገልጠው እየተናገሩ ረጅም ወራት መቀመጣቸውን በተናገረበት ክፍል የከተማውን ሕዝብ ሁኔታ ሲናገር «የከተማውም ሕዝብ ተከፍለው እኩሌቶቹ ከአይሁድ እኩሌቶቹ ከሐዋርያት ጋር ሆኑ» ይላል (የሐ.ሥራ14፡4)፤ እንደዚሁም በልስጥራን ጳውሎስና በርናባስን «አማልክት ሰዎችን መስለው ወደእኛ ወርደዋል» መባላቸውንና በዚያ የነበረው የድያ ካህን ከሕዝቡ ጋር ሆኖ ሊሠዋላቸው መውደዱን በሰሙ ጊዜ ልብሳቸውን ቀደው እየጮኹ ማስተዋቸውን ሲተርክ «ሐዋርያትም በርናባስና ጳውሎስ ግን ይህን በሰሙ ጊዜ ልብሳቸውን ቀደው ወደ ሕዝቡ መካከል እየጮኹ ሮጡ» ይላል (14፡14)፡፡ ሆኖም ጳውሎስ ሐዋርያ መሆኑን የሚያስረዱና ብቻውን ሐዋርያ ተብሎ የተጠራባቸው እጅግ ብዙ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅሶች ያሉ ሲሆን በርናባስ ግን ሐዋርያ ተደርጎ እንደተሾመም ሆነ ከጳውሎስ ጋር ሳይሆን ብቻውን ሐዋርያ ተብሎ እንደተጠራ የሚናገር አንድም የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል የለም፡፡ ደግሞም ጌታ ኢየሱስን በምድር ሳለ አላየውም፤ እንዲሁም ወደ አማኞች (ቤተክርስቲያን) የተቀላቀለው ከበዓለ ሃምሳ በኋላ በመሆኑ እና እንደ ጳውሎስም ከሙታን ተነሥቶ ያረገውን ክርስቶስን ያየ ባለመሆኑ የትንሣኤው የዓይን ምስክር ሊሆን አይችልም፤ ሆኖም ከሐዋርያው ጳውሎስ ጋር በሚሠራ ጊዜ ጳውሎስ እና እርሱ በአንድ ላይ ሐዋርያት ተብለው ሊጠሩ ችለዋል፤ በመሆኑም በዚህ አጠራር ውስጥ ሐዋርያነቱ የጳውሎስ እንጂ የበርናባስ አለመሆኑን መረዳት ያስፈልጋል፡፡
- ለ. 1ቆሮ4፡6፣9
በዚህ ጥቅስ ላይም ጳውሎስ ራሱን ከአጵሎስ ጋር አድርጎ «እኛ» ብሎ ይጠራል፤ ወረድ ብሎ በቊ.9 ላይ ደግሞ «እግዚአብሔር እኛን ሐዋርያቱን ...» ይላል፤ አጵሎስ ግን ጌታን በዓይኑ አላየም፤ የክርስቶስ የትንሣኤው የዓይን ምስክርም አይደለም፤ ሐዋርያ ተደርጎም በጌታ አልተሾመም፤ ለብቻውም ሐዋርያ ተብሎ የተጠራበትም አንድም ንባብ የለም፡፡ ስለሆነም አጠራሩ የመነጨው እንደ በርናባስ ሁሉ ከሐዋርያው ጋር አብሮ ከመሆኑና ከመሥራቱ የተነሣ እንጂ አጵሎስ በግሉ ሐዋርያ ስለነበረ አይደለም፡፡
- ሐ. 1ተሰ1፡1፣7
በዚህ ክፍል ደግሞ «የክርስቶስ ሐዋርያት እንደመሆናችን ...» የሚል ንባብ ይገኛል፤ ጳውሎስ 1ኛይቱን የተሰሎንቄ መልእክት የጻፈው ከስልዋኖስ (ሲላስ) እና ከጢሞቴዎስ ጋር እንደሆነ በምዕ.1፡1 ላይ እንረዳለን፡፡ ስለሆነም ራሱን ከእነርሱ ጋር አድርጎ ሐዋርያት ብሎ የጠራበት ምክንያት ስልዋኖስና ጢሞቴዎስ ሐዋርያት ስለሆኑ ሳይሆን ከእርሱ ጋር አብረው ስለሠሩ ነው፤ በተሰሎንቄ ከእርሱ ጋር አብረው መሥራታቸውን የሐ.ሥራ17፡1-15ን ስናነብ እንረዳለን፡፡ እነርሱ ግን በየግላቸው ጌታን አላዩም፤ የትንሣኤው የዓይን ምስክርም አይደሉም፤ ሐዋርያት ተደርገውም በራሱ በጌታ አልተሾሙም፤ ለየብቻቸውም ሐዋርያት ተብለው የተጠሩበት አንድም ስፍራ እንኳ የለምና እንደፊተኞቹ ሁሉ ይህም ጥቅስ ስልዋኖስና ጢሞቴዎስ ሐዋርያት ናቸው አይልም፡፡
- መ. ሮሜ16፡7
በዚህኛው ጥቅስ «በሐዋርያት መካከል ስመ ጥሩዎች ለሆኑ ደግሞም ክርስቶስን በማመን ለቀደሙኝ አብረውኝም ለታሰሩ ለዘመዶቼ ለአንዲራኒቆንና ለዩልያን ሰላምታ አቅርቡልኝ» የሚል ንባብ እናገኛለን፡፡ ከዚህ ጥቅስ በመነሣት አንዲራኒቆንና ዩልያን ሐዋርያት ነበሩ ለማለት ፈጽሞ አይቻልም፡፡ ምክንያቱም ንባቡ የሚለው «በሐዋርያት መካከል ስመ ጥሩዎች ለሆኑ» ነው እንጂ «ከሐዋርያት መካከል ለነበሩ» ወይም «ሐዋርያት ለነበሩት» አይልም፡፡ አንዲራኒቆንና ዩልያን ጳውሎስን ጌታን በማመን ይቀድሙታል፤ በሐዋርያት መካከልም የታወቁ ነበሩ፤ ከዚህም የተነሣ ንባቡ «በሐዋርያት መካከል (ዘንድ) ስመ ጥሩዎች» ሲል የታወቁ ማለትም ዝነኞች እንደነበሩ የሚያስረዳ ነው እንጂ እነርሱ ሐዋርያት መሆናቸውን የሚገልጽ አይደለም፡፡
ስለሆነም ጌታ እንደሾማቸው ከተመለከትናቸው ውጭ ሐዋርያት እንዳሉ የሚናገር ጥቅስ እንደሌለና ከላይ የተጠቀሱትም የሌሎችን ሐዋርያ መሆን የማያስረዱ መሆናቸውን ልንገነዘብ ያስፈልጋል፡፡ እነዚህንም ጥቅሶች የሚጠቅሱ ሰዎች ጥቅሶቹን የሚጠቅሱበት ዋነኛ ዓላማ የነስልዋኖስንና የሌሎችን ማንነት ማብራራት የግድ አስፈላጊ ሆኖ ሳይሆን ራሳቸውን በዚህ ሹመት ለማስገባት ቀዳዳ እንዲከፍትላቸው በብርቱ በመሻታቸው መሆኑ ከማንም የተሰወረ ሊሆን አይገባም፡፡
ቤተክርስቲያን በተመሠረተችበት በዚያን ዘመን ራስ የሆነው ጌታ ኢየሱስ ሐዋርያትን ለቤተክርስቲያን የሰጠው የእግዚአብሔር ቤት የሆነችውን የቤተክርስቲያንን መሠረት ለመጣል ነበር፡፡ እነዚህ የመሠረት ሥራ የተሠራባቸው ሐዋርያት ጌታን ያዩና በራሱ በጌታ ቀጥታ የተላኩ ሊሆኑ ይገባቸዋል፡፡ 12ቱን ሐዋርያት በተመለከተ ለሚመሰክሩት ነገር እነርሱን የተለየና የላቀ ተቀባይነት እንዲኖራቸው የሚያደርጋቸው ጌታ ኢየሱስን እና ትንሣኤውን አይተው የሚመሰክሩ መሆናቸው ነው፤ ይህንንም ዮሐንስ ሲናገር «ስለ ሕይወት ቃል ከመጀመሪያ የነበረውንና የሰማነውን በዓይኖቻችንም ያየነውን የተመለከትነውንም እጆቻችንም የዳሰሱትን እናወራለን፤ ሕይወትም ተገለጠ አይተንማል፤ እንመሰክርማለን..» ይላል (1ዮሐ.1፡1-2)፤ ጴጥሮስም ስለክርስቶስ ሞትና ትንሣኤ ለአሕዛብ በመሰከረ ጊዜ «እኛም በአይሁድ አገርና በኢየሩሳሌም ባደረገው ነገር ሁሉ ምስክሮች ነን፤ እርሱንም በእንጨት ላይ ሰቅለው ገደሉት፤ እርሱን እግዚአብሔር በሦስተኛው ቀን አስነሣው፤ ይገለጥም ዘንድ ሰጠው፤ ይኸውም ለሕዝብ ሁሉ አይደለም፤ ነገር ግን በእግዚአብሔር አስቀድሞ የተመረጡ ምስክሮች ለሆነን ለእኛ ነው እንጂ፤ ከሙታንም ከተነሣ በኋላ ከእርሱ ጋር የበላን የጠጣን እኛ ነን፡፡ ለሕዝብም እንድንሰብክና በሕያዋንና በሙታን ሊፈርድ በእግዚአብሔር የተወሰነ እርሱ እንደሆነ እንመሰክር ዘንድ አዘዘን» በማለት የሐዋርያነታቸውን ልዩ ባሕርያት በግልጽ ተናግሯል (የሐ.ሥራ10፡39-42)፡፡ ጳውሎስም ሐዋርያ የሆነበት ምክንያት አስቀድመን በስፋት እንዳብራራነው ያረገውን ጌታ በዓይን ስላየ፣ የትንሣኤው የዓይን ምስክር መሆን ስለቻለና በራሱ በጌታ ሐዋርያ ሊሆን የተጠራና የተሾመ ስለነበር ነው፡፡ ከ12ቱ ሐዋርያትና ከጳውሎስ በኋላ ግን በየስፍራው ወንጌል እየተሰበከ የሚያምኑ ሰዎች በዘመናት ሁሉ የእነርሱን ትምህርት መሠረት አድርገው በዚያው ላይ እንዲታነጹ እንጂ ሌላ ሐዋርያ እንዲኖራቸው ባለማስፈለጉ ጌታ ሌሎች ሐዋርያትን አልሾመም፡፡ በኤፌ.2፡20 ላይ «በሐዋርያትና በነቢያት መሠረት ላይ ታንጻችኋል» ተብሎ የተጻፈው ቃል የሚያረጋግጠውም ይህንኑ እውነት ነው፡፡ በዚህም መሠረት ከአምስቱ ስጦታዎች መካከል ሐዋርያትና ነቢያት የመሠረት ስጦታዎች እንደሆኑ በማያሻማ መልኩ መረዳት ይቻላል፡፡ አንድ ቤት መሠረቱ ከተጣለ በኋላ ቤቱ ወደ ላይ ያድጋል እንጂ ሌላ መሠረት አይጣልም፡፡ የሐዋርያት እና የነቢያት መሠረትም ሌላ ማንም ሳይሆን ራሱ ክርስቶስ ነው፡፡ በሐዋርያትና በነቢያት መሠረት ላይ ታንጻችኋል ሲልም ሐዋርያትና ነቢያት ኢየሱስ ክርስቶስን በተመለከተ ባስተማሩት ትምህርት ላይ መታነጻቸውን ያመለክታል፡፡ የእግዚአብሔር እስትንፋስ የሆኑ መለኮታዊ ቃላትም የተገለጡት የመሠረት ስጦታዎች በሆኑት በሐዋርያትና በነቢያት ነው፡፡
ጳውሎስ በኤፌ.3፡6 ላይ አሕዛብ በአንድ አካል አብረው የመሆናቸውና የመውረሳቸው ምስጢር የተገለጠው ለሐዋርያትና ለነቢያት መሆኑን በሚያስረዳ ጊዜ «... ለቅዱሳን ሐዋርያትና ነቢያት በመንፈስ አሁን እንደተገለጠ በሌሎቹ ትውልዶች ዘንድ አልታወቀም» ይላል፡፡ ከአምስቱ ስጦታዎች መካከልም ሁለቱን ለይተን በቤተክርስቲያን ምሥረታ ወቅት የነበሩ ስጦታዎች ናቸው ለማለት የምንችለው የእግዚአብሔር መንፈስ በዚያው በኤፌሶን መልእክት ውስጥ ሁለቱን ለይቶ በመጥቀስ የሐዋርያትና የነቢያት መሠረት አማኞች የሚታነጹበት እንደሆነና መለኮታዊ ምስጢራትም በእነዚህ ሰዎች እንደተገለጠ ስለነገረን ነው፡፡ ስለሆነም ከ2000 ዓመት በኋላም የእኛ ሐዋርያት እነዚያው የመጀመሪያዎቹ ናቸው እንጂ ሌሎች ሐዋርያት አይደሉም፡፡
እግዚአብሔር ወደ ሰው መግለጥ የሚፈልገውን ምስጢር ሁሉ በሐዋርያት በኩል ገልጦአል፤ ያም እስከ ዮሐንስ ራእይ ባሉት የአዲስ ኪዳን መጻሕፍት ተጽፎ ተጠናቅቋል፤ ስለዚህ እኛ ቀድሞ በእነዚያው ሐዋርያት የተባለውንና የተጻፈውን ትምህርት እና ትእዛዝ በመመሪያነት እንከተላለን እንጂ አዲስ መገለጥን ይዞ የሚመጣ ሐዋርያን አንጠብቅም፡፡ በይሁዳ መልእክት ቊ.17 ላይ «እናንተ ግን ወዳጆች ሆይ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ሐዋርያት ቀድሞ የተነገረውን ቃል አስቡ» የሚል ቃል እናነባለን፡፡ በመቀጠል በቊ.18 ላይ ደግሞ ማሰብ ያለባቸው ያ የሐዋርያት ቃል የትኛው እንደሆነ ሲናገር «እነርሱ፡ በመጨረሻው ዘመን በኃጢአተኝነት እንደ ገዛ ምኞታቸው እየሄዱ ዘባቾች ይሆናሉ ብለዋችኋልና» ይላል፡፡ ይህንንም የተናገረው ሐዋርያው ጴጥሮስ እንደሆነ ከ2ጴጥ.3፡3 መረዳት ይቻላል፡፡ ስለሆነም ሐዋርያት ሲባል በዚያን ጊዜ እንኳን የሚያመለክተው እነዚያኑ የጌታ ሐዋርያት ነበር፡፡ በእነርሱ በኩል የሚገኘው ትእዛዝ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ትእዛዝ ነው፤ ጴጥሮስ የሚጽፍላቸውን ሰዎች ልብ ለማነቃቃት «በቅዱሳን ነቢያት ቀድሞ የተባለውን ቃል በሐዋርያቶቻችሁም ያገኛችኋትን የጌታንና የመድኃኒትን ትእዛዝ እንድታስቡ በሁለቱ እያሳሰብኋችሁ ቅን ልቡናችሁን አነቃቃለሁ» በማለት ጽፏል (2ጴጥ.3፡2)፡፡ በዚህ ጥቅስ ውስጥ “በሐዋርያቶቻችሁ” ሲል ለመልእክቲቱ ተቀባዮች የተለዩ ሐዋርያት ነበሩ ለማለት ሳይሆን ከነዚያው ከመጀመሪያዎቹ የክርስቶስ ሐዋርያት ወደ እነርሱ ሄደው የሰበኩትን ሐዋርያት በተለይ የሚያመለክት ነው፤ ጳውሎስ ለምሳሌ ለቆሮንቶስ ሰዎች ሲጽፍ «የሐዋርያነቴ ማኅተም በጌታ እናንተ ናችሁና ለሌሎች ሐዋርያ ባልሆን ለእናንተስ ምንም ቢሆን ሐዋርያ ነኝ» እንዳለው ያለ ነው (1ቆሮ.9፡2)፡፡ እነዚህ ጴጥሮስ የጠቀሳቸው ሐዋርያት ከእርሱ ጋር የጌታ ሐዋርያት ከነበሩት መካከል እንደሆኑ የምንረዳው «በሐዋርያቶቻችሁም ያገኛችኋትን የጌታን የመድኃኒትን ትእዛዝ እንድታስቡ እያሳሰብኋችሁ» በማለት የጌታችንና የመድኃኒታችንን ትእዛዝ የያዙና ያስተላለፉ መልእክተኞች መሆናቸውን ስለገለጸ ነው፡፡
ሐዋርያት ሳይሆኑ ሐዋርያት ነን የሚሉ
በራእ.2፡2 ላይ «ሐዋርያት ነን የሚሉቱን መርምረህ ሐሰተኞች ሆነው እንዳገኘሃቸው አውቃለሁ» በማለት ጌታ ኢየሱስ በኤፌሶን ወዳለው ቤተክርስቲያን መልአክ የላከውን መልእክት እናነባለን፡፡ ጌታ ኢየሱስ በኤፌሶን ባለች ቤተክርስቲያን ካገኛቸው መልካም ነገሮች መካከል አንዱ ሐዋርያት ነን የሚሉትን መርምሮ ሐሰተኞች መሆናቸውን ማረጋገጡ ነበር፡፡ በዚያ በሐዋርያት ዘመን ከነበሩት የሐሰት አስተማሪዎች መካከል ብዙዎቹ ሐዋርያት ሳያዝዟቸውና ሳይልኳቸው ሐዋርያት አዝዘውናል ወይም ልከውናል በማለት በተለያዩ ከተሞችና መንደሮች በሚገኙ አጥቢያ ጉባኤያት እየዞሩ ተቀባይነት ለማግኘት ይሞክሩ ነበር (የሐ.ሥራ15፡24)፤ ይህ አልሳካ ያላቸው ደግሞ እንደ ክርስቶስ ሐዋርያት ተቀባይነትን ማግኘት ይችሉ ዘንድ በድፍረት «ሐዋርያት ነን» ይሉ ነበር፡፡ ይህንንም በተመለከተ ሐዋርያው ጳውሎስ ሲጽፍ «... እንደ እነዚህ ያሉ ሰዎች የክርስቶስን ሐዋርያት እንዲመስሉ ራሳቸውን እየለወጡ፣ ውሸተኞች ሐዋርያትና ተንኰለኞች ሠራተኞች ናቸውና፡፡ ይህም ድንቅ አይደለም፤ ሰይጣን ራሱ የብርሃንን መልአክ እንዲመስል ራሱን ይለውጣልና፡፡ እንግዲህ አገልጋዮቹ (የሰይጣን አገልጋዮች) ደግሞ የጽድቅን አገልጋዮች እንዲመስሉ ራሳቸውን ቢለውጡ ታላቅ ነገር አይደለም፤ ፍጻሜያቸውም እንደ ሥራቸው ይሆናል» (2ቆሮ.11፡13-15) ብሏል፡፡ ከዚህም እንደምንረዳው እነዚህ ሰዎች «ሐዋርያት ነን» የሚሉ ብቻ ሳይሆኑ የክርስቶስን ሐዋርያት እንዲመስሉ ራሳቸውን የሚለውጡ ተንኰለኞች ሠራተኞች ነበሩ፡፡ ያን ጊዜ የክርስቶስ ሐዋርያት በአገልግሎት ላይ ስለነበሩ በየስፍራው ያሉና በተለያዩ አማኞች በኩል ወንጌል የደረሳቸው ሰዎች የክርስቶስን ሐዋርያት ሁሉንም በዐይን ስላላዩአቸው ሊታለሉላቸው የሚችሉበት እድል እንዳለ በማሰብ ሐዋርያት ነን እያሉ የሐሰት ትምህርታቸውን ይዘሩ ነበር፡፡ በቆሮንቶስ በነበሩ አማኞች መካከል ብዙ ዓይነት መንፈሳዊ ውድቀት በመኖሩ ለእነዚህ ውሸተኞች ሐዋርያት የሐሰት ትምህርት የተጋለጡ ሰዎች እንደነበሩ ከ2ኛ ቆሮ.11 እንረዳለን፤ ሐዋርያው ጳውሎስ ግን እነዚህን ሰዎች የሰይጣን አገልጋዮች እንደሆኑ በመግለጥ ሥራቸውንም ሰይጣን የብርሃን መልአክ እንዲመስል ራሱን ከመለወጡ ጋር እያነጻጸረ ማንነታቸውን በመግለጥ በክፉ ትምህርታቸው የተታለሉትን ሁሉ በብርቱ ይወቅሳቸዋል፡፡
በቆሮንቶስ ቤተክርስቲያን ታይቶ የነበረው አጠቃላይ መንፈሳዊ ውድቀት በክርስትናው ዓለም እየታየ ባለበት በዚህ ዘመንም እነዚህ ውሸተኞች ሐዋርያትና ተንኰለኞች ሠራተኞች በዙሪያችን ይታያሉ፤ በአንዳንዶች ዘንድ «ከአባቶቻችን ከሐዋርያት ሲወርድ ሲዋረድ የመጣ ሐዋርያዊ ሥልጣንን ይዘናል» እየተባለ ሲነገር ከምንሰማው ጀምሮ በግልጽ «ሐዋርያት ነን» ብለው እስከተነሡትና «ሐዋርያው እገሌ» እየተባሉ ለመጠራት እስከደፈሩት ድረስ በውሸተኞች ሐዋርያት የተበከሉ አገልግሎቶች እያየን ነው፡፡ በእጅጉ የሚያሳዝነው ደግሞ እግዚአብሔር የቀባኝ ሐዋርያ ነኝ ብሎ በድፈረት የተነሣውን ሁሉ ሙሉ በሙሉ በመቀበል ወደፈለገው እንዲነዳቸው ራሳቸውን አሳልፈው የሰጡት የብዙ ሰዎች ጉዳይ ነው፤ «እንደ ገዛ ምኞታቸው ለራሳቸው አስተማሪዎችን ያከማቻሉ» (2ጢሞ.4፡3) እንደተባሉት ሰዎች በሚመቻቸውና የሥጋ አርነት ባለበት መንገድ የሚመራቸውን፣ እነርሱም የሚፈልጉትን መገለጥ ከልቡ አንቅቶ የሚናገርላቸውን ሐዋርያ ሾመው የሚከተሉትና ለትእዛዙም የሚገዙለት ጥቂቶች አይደሉም፤ ሐዋርያ ነኝ ብሎም በድፍረት የተገለጠው ሰው በዚህ የተነሣ የሚያገኘው ነውረኛ ረብ (ጥቅም) እና ክብር ኅሊናውን ስላሳወረው በውሸት ላይ ውሸትን በሐሰት ትምህርት ላይ ሌላ የሐሰት ትምህርትን እየደራረበ ወደ ወደደው ሲወስዳቸው ምንም አይሰማውም፤ ተከታዮቹም አንድ ጊዜ «ሐዋርያ» ብለው ከፍ ያደረጉትን ሰው መመርመር እንደ ድፍረት ቈጥረው በእርሱ ስሜትና ኅሊና እየተመሩ ሲሄዱ ይኖራሉ፡፡ አቤት እንዴት ያለ ድንዛዜ ነው! እንዴትስ ያለ አለማስተዋል ነው! ሐዋርያት ነን የሚሉት በየዕለቱ በሕዝብ ፊትም ሆነ ከዚያ ውጪ የሚሠሩት የተገለጠውን መጽሐፍ ቅዱሳዊ ያልሆነ ሥራና አካሄድ እያዩ ከዚህ ዓመፃ አለመለየትስ እንዴት ያለ ግርዶሽ ነው!
በሐዋርያትና በነቢያት መሠረት ላይ የታነጹ አማኞች ግን እንደ እነዚህ ያሉ ሰዎች ሐዋርያት ነን ብለው ሲነሡ እንደ ኤፌሶን ቤተክርስቲያን መርምረው ሐሰተኞች መሆናቸውን ወዲያውኑ ይረዳሉ፤ የሚመረምሩበት መንገድም በጣም ግልጽ ነው፤ ሐዋርያ የሆነ ሰው ጌታን በዓይን ያየ መሆን አለበት፤ የትንሣኤው የዓይን ምስክር ሊሆን ግድ ነው፤ በራሱ በጌታ ሐዋርያ ተደርጎ የተሾመ ሊሆንም ያስፈልገዋል፡፡ ሐዋርያት ነን የሚሉትም ሆነ የሐዋርያትን ሥልጣን ተቀብለናል የሚሉት ሁሉ ግን ይህ ሁሉ ስለሌላቸው ሐሰተኞች መሆናቸው ወዲያው ይታወቃል፡፡ ከዚያ ይልቅ የቀደሙት ሐዋርያት ያስተማሩት ሁሉ በአዲስ ኪዳን መጻሕፍት ተጽፈው ስለሚገኙና ለእኛ የተሰጠው የእግዚአብሔር መገለጥም ተጽፎ የተጠናቀቀ በመሆኑ ሁልጊዜ በሐዋርያት ትምህርት ልንተጋ ይገባል (የሐ.ሥራ2፡12)፡፡ በጌታ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ተሰብስበን ሐዋርያት የጻፉትን መጻሕፍት በጋራ ስናጠናም ሆነ ጌታ የአስተማሪነት ጸጋ በሰጣቸው ወንድሞች መጽሐፍ ቅዱስን ስንማር በሐዋርያት ትምህርት እየተጋን መሆኑ ሊታወቅ ይገባል፡፡ ይህንንም ስናደርግ ሐዋርያው ዮሐንስ እንዳለው ከእነርሱ ከሐዋርያት ጋር ኅብረት እያደረግን ነው (1ዮሐ.1፡3)፡፡
ነቢያት